ሚያዝያ 11 ቀን 2002 ዓ.ም.
የብፁዕ አቡነ ልሳነ ክርስቶስ ቅብዓተ ጵጵስና ተከናወነ
- ብፁዕ ወቅዱስ ርዕሰ ሊቃነጳጳሳት ቤኔዲክቶስ 16ኛ
የተመረጡበት አምስተኛ ዓመት ተከብሯል
የብፁዕ አቡነ ልሳነክርስቶስ የአዲስ አበባ ካቶሊካዊ ሰበካ ረዳት ጳጳስ ቅብዓተ ጵጵስና ዕሁድ ሚያዝያ 10 ቀን 2002 ዓ.ም አዲስ አበባ ካቶሊክ ካቴድራል በብፁዕ አቡነ ብርሃነየሱስ ሊቀጳጳሳት ካቶሊካውያን ዘኢትዮጵያ እጅ በደማቅ መንፈሳዊ ስነሥርዓት ተከናውኗል፡፡
ብፁዕነታቸው ከማለዳው በ1፡15 በብፁዓን ጳጳሳት፣ ቁጥራቸው በርካታ በሆነ ካህናት፣ መዘምራን፣ የብፁዕነታቸው ቤተሰብና ምዕመናን ታጅበው የዑደት ሥነስርዓት የተካሄደ ሲሆን በስነስርዓቱ ላይ ብፁዕ አቡነ ጢሞቲዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የቅድስት ስላሴ ኮሌጅ ጳጳስ/ዲን ክቡር አቶ ግርማ ብሩ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚንስትር፣የተለያዩ ሃይማኖቶች፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ካቶሊካዊ ተቋማት ተወካዮች ተገኝተው ነበር፡፡
ብፁዕ አቡነ ብርሃነየሱስ ለቀጳጳሳት ካቶሊካውያን ዘኢትዮጵያ ቅብዓተ ጵጵስናውን በሰጡበት ወቅት ባሰሙት ቃለምዕዳን ለእግዚአብሄር ምስጋና ይድረሰው ካሉ በኋላ ዛሬ የምናከብረው በዓል የብፁዕ አቡነ ልሳነ ክርስቶስን ጵጵስና ብቻ ሳይሆን ርዕሰ ሊቃነጳጳሳት ቤኔዲክቶስ 16ኛ የተመረጡበትን አምስተኛ ዓመት ጭምር ነው፡፡ ብለዋል፡፡ አስከትለውም “ብፁዕ አቡነ ልሳነ ክርስቶስ የተገኙት ከካህናት ነው ስለዚህም ካሕናትን አመሰግናለሁ፡፡ በዚሕ የካህናት ዓመት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ 16ኛ ለካሕናት የስተላለፉትን መልዕክት ላስታውስ እወዳለሁ፡፡ ካህናት ልጆቼ ሆይ ህይወታችሁን የሰጣችሁት ለክርስቶስ ነው ለሰው አይደለም፡፡ ስለዚህ ለክርስቶስ ታማኞች ሁኑ ለቤተክርስቲያንም ታማኝ አገልጋዮች ሁኑ ብለው አደራቸውን ጥለውባቸዋል፡፡ ህይወቱን ለክርስቶስ የሰጠ እውነተኛ ሐዋሪያ ጥሪውን ይዞ ሳይፈራ ምዕመንን ያገለግላል፡፡ ምዕመናንም ካህናት የወጡት ከናንተ ስለሆነ ካህናትን የምታስከብሯቸውና የምታከብሯቸው እናንተ ምዕመናን ናችሁ፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓመት ካህናት በየሰበካው የተአዝዞ ቃላቸውን ያድሳሉ፡፡ ለጳጳሳትና ለቤተክርስቲያን ለመታዘዝ ብቻ ሳይሆን ምዕመናንን ለማገልገል፡፡ በዛሬው ዕለት ደግሞ በተለይ ከካህናት ቀጥሎ ምዕመናንን አመሰግናለሁ፡፡ እዚህ የምታይዋቸው ጳጳሳት፣ ካህናትና ደናግል ሁሉ የተገኙት ከናንተ ነው፡፡ በምስጢረ ተክሊል የተመሰረተና የጸና ቤተሰብ ባለ ቁጥር ጥሪ ይገኛል፡፡” ብለዋል፡፡ በመጨረሻም ለብፁዕ አቡነ ልሳነክርስቶስ “የመረጠዎት መንፈስ ቅዱስ ነው የሚያጸናዎትም መንፈስ ቅዱስ ነው” በማለት በጸሎት እንዲበረቱ አደራ ብለዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ልሳነክርስቶስ በበኩላቸው በሲመተ ጵጵስናው ላይ የተገኙትን ሁሉ “ታላቅ ደስታ ስለተሰማኝ የልቤን ምስጋና ልገልጽላችሁ እወዳለሁ” ብለዋል፡፡ አያይዘውም “እኔም ይህንን ታላቅ ኃላፊነት ስቀበል በራሴ ዕውቀትና ብቃት በመተማመን ሳይሆን በእግዚአብሄር የጸጋ ስጦታዎች እርዳታ የእግዚአብሄር ነገር ግድ በሚላቸው በእመቤታችንና ቅዱሳን አማላጅነት በመላዋ ቤተክርስቲን ጸሎትና መልካም ፈቃድ ባላቸው የሃገራችን ዜጎችና የመንግስት ኃላፊዎች ድጋፍ ተስፋ በማድረግ እወጣዋለሁ በሚል ጥልቅ እምነት ነው፡፡” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ጽ/ቤት
ማኅበራዊና ህዝብ ግንኙነት ማስተባበሪያ

 |